ክልላዊ የህብረተሰብ ጤና ድንገተኛ አደጋዎች ጭምጭምታ መሰብሰቢያ በይነ መረብ ተዘጋጀ፤ መጋቢት 4/2018ዓ.ም የክልሉ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ያስለማው የህብረተሰብ ጤና ድንገተኛ አደጋዎች ጭምጭምታ መሰብሰቢያ በይነ መረብ ርክክብ ተካሄደ። ክልላዊ የጤና በይነ መረብ ርክክብ ያካሄዱት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ማሙሽ ሁሴን እና የክልሉ ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ቢሮ ሃላፊ አቶ ሰላሙ አማዶ ናቸው። በርክክብ ፕሮግራሙ የኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ማሙሽ ሁሴን በክልልም ሆነ በሀገር ደረጃ በየጊዜው የሚነሱ ወረርሽኞችን በብቃት የመከላከል አቅም እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል።
በዘርፉ ትልቅ መሻሻሎች መምጣታቸውንም ጠቅሰው፣ለአብነትም በቅርብ ዓመታት ማልበርግ፣ኮሌራ፣ወባና የመሳሰሉ ወረርሽኞችን ለመከላከል እንደ ክልልም ሆነ እንደ ሀገር የተደረጉ ርብርቦች ውጤታማ እንደነበሩም አመላክተዋል። ሆኖም በስራዎቹ ላይ ወቅታዊ የወረርሽኝ መረጃ ቀድሞ የማግኘት ችግሮች እንዳሉም አመላክተዋል ፣እነዚህን ችግሮች የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ለመፍታት እየተሰራ እንደሚገኝም አስረድተዋል። ይህንን ችግር ለመፍታትም ዛሬ ርክክብ የተደረገው በይነ መረብ ከፍተኛ እገዛ እንደሚኖረውም የገለጹት አቶ ማሙሽ፣ቴክኖሎጂውን በመጠቀም ቀድሞ የወረርሽኝ መረጃ በማሰባሰብ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት የላቀ እገዛ እንደሚኖረውም አስታውቀዋል።
በይነ መረቡ የክልሉን ወረርሽኝ የመመከት አቅም የሚያሳድግ፣የመረጃ መዘግየትን የሚያስቀር፣ ለህብረተሰቡ በቀላሉ ተደራሽ የሚሆን፣በክልሉ ሁሉም መዋቅሮችና ከሌሎች አካባቢዎች ጭምር የሚከሰቱ የወረርሽኝ ስጋቶችን ቀድሞ በመገንዘብ የህብረተሰብ ጉዳትን በከፍተኛ ደረጃ መቀንስ ያስችላል ብለዋል አቶ ማሙሽ። የለማው ቴክኖሎጂ የሪፖርት መዘግየትን የሚያስቀር፣ለአጠቃቀም ምቹና ቀላል ፣በእያንዳንዱ ቀበሌና ጎጥ ያለውን አጠቃላይ የወረርሽኝ መረጃ በፍጥነት የሚገልጽ፣ወቅታዊ መረጃ ለህብረተሰቡ ማድረስ የሚያስችል እንደሆነም ዋና ዳይሬክተሩ አብራርተዋል።
የክልሉ ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ቢሮ ሃላፊ አቶ ሰላሙ አማዶ በበኩላቸው ቴክኖሎጂው የመረጃ ዘላቂነትን በቀጣይ የሚያረጋግጥ ስለመሆኑም ገልጸዋል። የለማው በይነ መረብ በክልሉ የጥናትና ምርምር ስራዎች እንዲጠናከሩ የሚያደርግ፣ጊዜና ወጭን የሚቀንስ፣ የመረጃ ጥራትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ እገዛ እንዳለውም ቢሮ ሃላፊው አስታውቀዋል። ቴክኖሎጂው ህብረተሰቡን ከወረርሽኝ እንዲጠበቅ ትምህርት መስጠት የሚያስችልና ጤናውን በመጠበቅ በተሰማራበት የስራ መስክ ውጤታማ መሆን እንዲችል ጥሩ አማራጭ ስለመሆኑም አቶ ሰላሙ ገለጻ አድርገዋል። በይነ መረቡ የለማው በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት እና በክልሉ ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ቢሮ በመተባበር ነው።