Skip to main content
zena61

የሳይበር ጥቃት መከላከል ወትሮ ዝግጁነት በማረጋገጥ ረገድ በጋራ መስራት እንደሚገባ ተጠቆመ። ስኬታማ እና ዘላቂ የሳይበር መከላከል ወትሮ ዝግጁነት በማረጋገጥ ረገድ በጋራ መስራት እንደሚገባ ተጠቆመ፡፡ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) ሀገራዊ የሳይበር ጥቃት መከላከል ወትሮ ዝግጁነት ላይ ያተኮረ ውይይት ከተለያዩ ባለድሻ አካላት ጋር (የጸጥታና ደህንነት ተቋማት፣ ቁልፍ መሰረተ ልማት የሚያስተዳድሩ ተቋማት፣ የፋይናንስ ተቋማት፣ ሚዲያ ወ.ዘ.ተ) አካሂዷል፡፡ የውይይት መድረኩን በንግግር የከፈቱት የኢመደአ ም/ዋና ዳይሬክተር ተወካይ አቶ ሃኒባል ለማ እንዳሉት ሀገራችን አሁን ካለችበት ወቅታዊ የጂኦ-ፖለቲካል ሁኔታ አኳያ፤ በተለይም ከታላቁ የህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ጋር ተያይዞ የውስጥና የውጭ ስጋቶች መበራከትን ተከትሎ ተቋማት የሳይበር ደህንነታቸውን ከመጠበቅ አኳያ አስፈላጊውን የጥንቃቄ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባቸው ገልጸዋል፡፡ ሀገራዊ የሳይበር ደህንነትን ማረጋገጥ የሚቻለው ተቋማት የራሳቸውን የሳይበር ደህንነት ማረጋገጥ ሲችሉ እንደሆነ የጠቆሙት አቶ ሃኒባል፤ ከዚህ አኳያ ተቋማት ያላቸውን የዲጂታል ሃብት እና መሰረተ ልማት በአግባቡ መለየትና የአደጋ ግምገማ (Risk Assessment) ማካሄድ፤ የ24/7 የክትትልና ምላሽ አቅምን ማሳደግ፣ የሰራተኞችን ግንዛቤ በተከታታይ ስልጠና ማሳደግ፣ እንዲሁም ማንኛውንም የጥቃት ሙከራ ለብሔራዊ የሳይበር ደህንነት ማስተባበሪያ ማዕከል ሪፖርት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ በመጨረሻም ከተሳታፊዎች ለተነሱ አስተያየትና ጥያቄዎች ሰፊ ማብራሪያና ምላሻ ከመድረኩ የተሰጠ ሲሆን፤ ወጥነት ባለው መልኩ እንዲህ ዓይነት መድረኮች እንደሚካሄዱና በቀጣይ ሁሉም ተቋማት እንደሚሰጡት የአገልግሎት ዓይነትና ስፋት በሚቀመጠው መስፈርት ልክ የሳይበር መከላከል ከፍል ሊኖራቸው እንደሚገባ ተመላክቷል፡፡